በሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የሐዋሳ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የ2013 ዓ.ም የእቅድ አፈጻጸም ግምገማ እና የ2014 በጀት አመት እቅድ ከባለድርሻ አካላት ጋር የምክክር መድረክ አደረገ።

በሲዳማ ብሔራዊ ክልል የሐዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ረ/ፕሮፌሰር ጸጋዬ ቱኬ ከተማ አስተዳደሩ የራሱን ወጪ በራሱ ገቢ የሚሸፍን መሆኑን አስታውሰው የተጀመሩና በዕቅድ የተያያዙ ትላልቅ ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ እና የከተማውን ኢንቨስትመንት ለማሳደግ ገቢን በቁርጠኝነት ለመሰብሰብ ከወትሮው በተለየ መንገድ እንደሚሰራ ገልጸዋል።

የሐዋሳ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ቅርንጫፍ ጽ/ቤት አቶ ታምሩ ተፈሪ እንደገለጹት በበጀት አመቱ በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ተግባራትን ከዳር ለማድረስ የህዝብ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ምላሽ ለመስጠት መስሪያ ቤቱ በ2013 በጀት ዓመት እንደ ከተማ 2 ቢሊየን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ ብር 1.781 ቢሊየን ማሳካት እንደተቻለ ገልጸዋል።

ከ2012 በጀት ዓመት ጋር ሲነፃፀር ብር 443 ሚሊየን በላይ ብልጫ ቢኖረውም የከተማውን ገቢ ከመሰብሰብ አንፃር በርካታ ቀሪ ስራዎች መኖራቸውን ተናግረዋል።

በ2014 በጀት ዓመት ብር 2.6 ቢሊዮን እንደሚሰበሰብ መታቀዱንም ኃላፊው ተናግረዋል።

ከገቢዎች በለስልጣን ዋና ቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ 2013 በጀት ዓመት ከከተማ አቀፍ የሴክተር መ/ቤቶች በአፈጻጸም ግምገማ 2ኛ ደረጃ እንዳገኘ ተገልጿል።

በመድረኩ የተሳተፉ ባለሙያዎች የገቢ አሰባሰብ ስርዓትን በማዘመን በከተማዋ የታቀዱ ታላላቅ ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው ዕቅድ መሰረት ለማከናውን እና ኢንቨስትመንትን ለማሳደግ በቁርጠኝነት እንደሚስራ ገልጸው የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ገቢ ሰብሳቢ መ/ቤቱን በሁሉ መደገፍና ከጎናቸው እንዲቆሙ ጥሪ አድርገዋል።

ከገቢዎች በለስልጣን ዋና ቅርንጫፍ ጽ/ቤት እንዲሁም በክ/ከተማ በእቅድ አፈጻጸም ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገበው ሠራተኞች የዋንጫ፣ የሜዳሊያ፣ የገንዘብ፣ ኮምፒውተር ፣ የፕሪንተር እና የሴርተፍኬት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።

ሐ/ከ/አሐ/ከ/አ/መ/ኮ/ጉ/መምሪያ

ነሐሴ 26/2013 ዓ.ም

ሐዋሳ

Share this Post