የሐዋሳ አዳሬ አጠቃላይ ሆስፒታል የሰራተኞች ፎረም እና የ2014 ዓም የአንደኛ ሩብ ዓመት የስራ አፈፃፀም ግምገማ አካሄደ።

በግምገማ መድረኩ የተሻለ አፈፃፀም ላስመዘገቡና ለተቋሙ የስራ መቃናት የበኩላቸውን ለተወጡ የተቋሙ ሰራተኞች እውቅና የመስጠት ስራ የተከናወነ ሲሆን የደም ልገሳ መርሀግብርም ተካሂዷል።

በሩብ ዓመቱ የስራ አፈፃፀም የግምገማ መድረክ የተቋሙን የ2014 ዓም የመጀመሪያ ሩብ ዓመት አጠቃላይ የስራ እንቅስቃሴ የሚያሳዩ ሪፖርቶች ቀርበው ሰፊ ውይይትም ተካሂዷል።

በሰሜኑ የሐገራችን ክፍል በተፈጠረው አለመረጋጋት የተለያዩ ችግሮች ላጋጠማቸው እና ከቤት ንብረታቸው ለተፈናቀሉ የህብረተሰብ ክፍሎች እንደተቋም ድጋፍ እናድርግ በሚሉ ጉዳዮች ዙሪያ የተቋሙ ሰራተኞችና የማኔጅመንት አባላት የመከሩ ሲሆን በፈቃደኝነት ግንባር ድረስ በመሄድ የህክምና እርዳታ ከመስጠት ጀምሮ የገንዘብና የቁሳቁስ ድጋፍ በማድረግ ለሀገር መከላከያ ሰራዊትና ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች አለኝታ ለመሆን እንቅስቃሴ መጀመሩም ተመላክታል።

እንደ ተቋም በጥንካሬ የተመዘገቡ በርካታ የተሻሉ አፈፃፀሞች መመዝገባቸውን የገለፁት የመድረኩ ተሳታፊ የተቋሙ ሰራተኞች በቀጣይ ሊሻሻሉና አፋጣኝ ማስተካከያ ሊደረግባቸው ይገባል ያሉዋቸውን ጉድለቶች በማንሳት የጋራ መፍትሄ ማስቀመጥ የሚያስችል ሰፊ ውይይትም አካሂደዋል።

አቶ ፍሬው ሀንቄ የሐዋሳ አዳሬ አጠቃላይ ሆስፒታል ዋና ስራ አስኪያጅ በመድረኩ ባስተላለፉት መልዕክት የሰራተኞች ፎረም እና የአንደኛ ሩብ ዓመት የስራ አፈፃፀም የግምገማ መድረኩ ባለፉት ሶስት ወራት የታዩ ጠንካራ አፈፃፀሞችን አጠናክሮ ለማስቀጠል እና የታዩ ክፍተተቶችን አርሞ በቀጣይ የተሻለ አፈፃፀም ለማስመዝገብ ያለመ መሆኑንም ጠቁመዋል።

በ1954 ዓም የተቋቋመው የሐዋሳ አዳሬ አጠቃላይ ሆስፒታል ከተመሰረተ 60ኛ ዓመቱ ላይ እንደሚጉኝ የገለፁት የተቋሙ ስራ አስኪያጅ አቶ ፍሬው ሀንቄ ለከተማው ነዋሪ እና ለአጎራባች አካባቢ ህዝቦች ከፍተኛ ግልጋሎት እየሰጠ ደረጃ በደረጃ እያደገ ከክሊኒክነት ወደ ጤና ጣቢያ ከዚያም ወደ መጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታልነት በመቀጠልም ከ2008 ዓም ወዲህ አጠቃላይ ሆስፒታል ደረጃ መድረሱንም አስታውሰዋል።

የሐ/ከ/አስ/የመ/ኮ/ጉ/መምሪያ

ጥቅምት/19/2014ዓም

ሐዋሳ

Share this Post