የሐዋሳ ከተማ ነዋሪ ለመከላከያ ሰራዊት 70.8 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት ድጋፍ አደረገ።

የሐዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ረዳት ፕሮፌሰር ፀጋዬ ቱኬ ድጋፉን አስመልክቶ እንደተናገሩት የእዉነተኛ የሀገር ልጅነት መታያው ሀገር በእንዲህ አይነት ችግር ውስጥ ስትወድቅ ነው ብለዋል።

ከንቲባው አክለውም ለነገ ሀገር ተረካቢ ትውልድ የጸዳች ኢትዮጵያን ለማሰረከብ አሁን የገጠመንን ችግር በጋራ መታገል ሲቻል ብቻ እንደሆነም ገልፀዋል።

በዚህ ረገድ አሉ ከንቲባው ኢትዮጵያ በዚህ ወሳኝ ወቅት ጭንቋን የሚጨነቁላት ምጧን የሚያምጡላት የጀግኖች መፍለቂያነቷ መሆኗን ልክ እንደ ትናንቱ ሁሉ ዛሬም ጀግኖች ልጆች አላት ብለዋል።

የሐዋሳ ከተማ ነዋሪም የዚህ ውድ ኢትዮጵያዊ ጀግና አካል በመሆን ካለው ላይ ሳይሳሳ ያደረገው ድጋፍ ትልቅ ክብር እንዲሰጠው የሚያደርገው እንደሆነም ነው ከንቲባ ፀጋዬ ያስረዱት።

የከተማዋ ነዋሪ 70.8 ሚሊዮን ብር የሚገመት በአይነትና በገንዘብ ድጋፍ አድርጓልም በማለት ነው ከንቲባ ፀጋዬ ቱኬ የገለፁት።

የከተማዋ ነዋሪ ድጋፍ በዚህ ብቻ የተገታ አለመሆኑን የጠቆሙት ከንቲባው ግንባር ድረስ ለፀጥታ ሀይሉ ደጀን ለመሆን እስከመዝመት የደረሰ ቁርጠኝነቱንም ማሳየቱን ተናግረዋል።

አሸባሪው የህወሀት ቡድን በሀገራችን ላይ የጋረጠውን አደጋ ለመቀልበስ ክቡር ጠቅላይ ሚንስትር አብይ አህመድ ግንባር ድረስ በመዝመት ያሳዩት ፍፁም የሆነ ኢትዮጵያዊነት ሌሎችንም ያነሳሳ ስለመሆኑም ከንቲባው ተናግረዋል።

የሐዋሳ ከተማ ነዋሪዎች በየትኛውም ወቅት ጥሪ በሚደረግበት ወቅት ምላሽ በመስጠት አንድነታቸውን በማሳየት ላደረጉት ብርቱ ወገንተኝነትም ከንቲባው ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

ሐዋሳ ከተማ አስተዳደር ብልጽግና ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ ካሱ አሩሳ በበኩላቸው ኢትዮጵያ ከገባችበት ችግር ለማዳን እና ህልውናዋን ለማረጋገጥ የከተማዋ ነዋሪ የበኩላቸውን ድጋፍ እያደረጉ ይገኛል ብለዋል።

በዚህም አሉ አቶ ካሱ ነዋሪው 62 ሰንጋ፣ 59 ኩንታል በሶ፣ የምግብ ፍጆታ እንዲሁም አልባሣት በአይንት 60 ሚሊዮን እንድሁም በገንዘብ 10.8 ሚሊዮን ብር እና ከመንግስት በአጠቃላይ 70.8 ሚሊዮን ድጋፍ ማድረጋቸውን አስረድተዋል።

አቶ ሚልክያስ አንዴቦ የሐዋሣ ከተማ ንግድ እና ዘርፍ ማህበራት ም/ቤት ሰብሣቢ በበኩላቸው አሸባሪ የህወሀት ቡድንን ለማጥፋት እየተደረገ ያለውን ርብርብ ምክር ቤቱ የንግዱን ማህበረሰብ በማስተባበር በአይነትና በገንዘብ 13.9 ሚሊዮን ድጋፍ ማድረግ ችሏል ብለዋል።

ይህ የንግዱ ማህበረሰብ ድጋፍ በቀጣይም ሀገር ከወራሪው የህወሀት ቡድን ነፃ እስክትወጣ ድረስ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ነው የከተማዋ ንግድ እና ዘርፍ ምክርቤት ሰብሳቢ ተናግረዋል።

በዚህ የድጋፍ መርሀግብር ላይ ከተገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች መካከል ልጆቻቸውን ወደ ሀገር መከላከያ የላኩ እናቶች ተገኝተዋል።

እንደ እናቶቹ ገለፃ ሀገር ከሌለ መኖር እንደማይቻልና ኢትዮጵያን የደፈረ የሀገርም ሆነ የውጭ ጠላት ለመመከት ልጆቻቸውን መርቀው መላካቸውን ተናገረዋል።

ይህ የእናቶቹ ለሀገር ደጀን መሆን በቀጣይም ለሰራዊቱ ስንቅ በማዘጋጀት ጭምር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስረድተዋል።

የሐ/ከ/አስ/የመ/ኮ/ጉ/መምሪያ

ህዳር 19/2014 ዓ.ም

ሐዋሳ

Share this Post