የሐዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ረ/ኘሮፌሰር ፀጋዪ ቱኬ በሐዋሳ ዙሪያ ወረዳ ቃሬሶ ዴላ ጤና ጣቢያ ግንባታ አስጀመሩ።

ከንቲባው ከወራቶች በፊት የመሰረተ ድንጋይ በማስቀመጥ በገቡት ቃል መሰረት ነው ዛሬ የግንባታ ስራውን ያስጀመሩት።

ለአካባቢው ህብረተሰብ በጣም አስፈላጊ የሆነው ይህ ጤና ጣቢያ የበርካታ ወላድ እናቶችንና ህጻናትን ህይወት የሚታደግ ከመሆኑም በላይ የህብረተሰቡን እንግልት የሚቀርፍ ነው ብለዋል።

ይህ ኘሮጀክት የሐዋሳ ህዝብ ለአካባቢው ህብረተሰብ የሰጠው ስጦታ ነው ያሉት ከንቲባ ጸጋዬ በቀጣይም በሌላ ኘሮጀክት ስራ የሚጠናከር ይሆናል ብለዋል።

የሐዋሳ ከተማና ሐዋሳ ዙሪያ ወረዳ በብዙ ነገሮች የሚገናኙ ሲሆን ከተማና ገጠሩ በአንድነት ተሳስረው እንዲያድጉ ይፈለጋልም ነው ያሉት።

የአበራ ልሳኑ ህንጻ ተቋራጭ ስራአስኪያጅ የሆኑት አቶ አንተነህ ቡርቃ ከ3 ቀናት በፊት ርክክብ የተደረገ መሆኑን ገልጸው ግንባታውን በ3 ወራት ውስጥ ለማጠናቀቅ እንደሚሰሩ ነው የተናገሩት።

የጥራት ደረጃውን በጠበቀ መልኩ እንደሚሰሩ የተናገሩት አቶ አንተነህ ለዚህም በቂ ዝግጅት መደረጉን አስረድተዋል።

የአካባቢው ነዋሪዎች በበኩላቸው ከዚህ ቀደም የመሰረተ ልማት፣ የውሃ፣ የት/ቤቶችና ሌሎችም ችግሮች እንደነበረባቸው ተናግረው ይህም ደረጃ በደረጃ እየተመለሰ መምጣቱን ገልጸዋል።

አሁን ላይ ደግሞ በእጅጉ የሚፈልጉት የጤና ጣቢያ ግንባታ ስራ መጀመሩ እንዳስደሰታቸውም አክለዋል።

ይህ ጤና ጣቢያም 7 ቀበሌያትን የሚያዋስን በመሆኑ እነዚሁ ቀበሌያትን የአገልግሎቱ ተጠቃሚ እንደሚያደርጋቸው ነው ነዋሪዎቹ ያስረዱት።

የሐ/ከ/አስ/የመ/ኮ/ጉ/መምሪያ

ህዳር 7/20114

ሐዋሳ

Share this Post