የሐዋሳ ከተማ የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ የአምስት ወራት እቅድ አፈጻጸሙን ገመገመ።

በዚህ የአምስት ወራት አፈፃፀሙን በገመገመት መድረኩ መምሪያው በአዲስና በነባር ፍቃድ እድሳት እንዲሁም ያለ ንግድ ፍቃድ የሚከናወኑ የንግድ ስራዎችን ከመከላከል አንፃር የላቀ ውጤት መገኘቱ ተጠቁሟል።

የሐዋሳ ከተማ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ሀይሉ የተራ እንደገለፁት በሩብ አመቱ በከተማዋ የሚሰሩ የንግዱ ማህበረሰብ አባላት ህጋዊ አሰራርን ተከትለው እንዲሰማሩ ከማድረግ አንፃር አበረታች ስራ ተከናውኗል ብለዋል።

ደረሰኝን መነሻ ያደረገ የዋጋ ቁጥጥር፣ በህገወጥ ምርት ክምችት፣ የተሻለ አፈጻጸም መኖሩንም ነው ሀላፊው ያስረዱት።

በህገ ወጥ የታሸጉ ምግቦችና መጠጦች ላይ የሚደረጉ የዋጋ ጭማሬዎችንም አስመልክቶ መምሪያው በያዝነው ወር ባደረገው ክትትል ጠንከር ያለ እርምጃ መወሰዱንም ሀላፊው አስረድተዋል።

አቶ ሀይሉ ከፍጆታ እቃዎች ምርት እጥረት ጋር ተያይዞ ችግር መኖሩን ገልጸው ከባለድርሻ አካላት ጋር የተለየ ቅንጅታዊ ስራ ካልተሰራ የሚፈለገው ለውጥ ለማምጣት እንደማይቻልም ነው የገለፁት።

በግምገማ መድረኩ የተገኙ ባለ ድርሻ አካላት በተለይም ከንግድ ፍቃድ፣ ከነዳጅ፣ ከፍጆታ እቃ ጋር ተያይዞ ሊታረሙ እንደሚገባ ተናግረዋል።

ከአገልግሎት አሰጣጥ አንፃርም የሚስተዋሉ ችግሮችን በተጠናከረ መልኩ ተግባራዊ ማድረግ በሚቻልበት ረገድም ባለ ድርሻ አካላቱ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

የሐ/ከ/አስ/የመ/ኮ/ጉ/መምሪያ

ታህሣስ 10/2014 ዓ/ም

ሐዋሳ

Share this Post